በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የቤተሰብ ሕይወትን አስደሳች ለማድረግ የሚረዳ ጥበብ

የቤተሰብ ሕይወትን አስደሳች ለማድረግ የሚረዳ ጥበብ

ትዳርና ልጆች፣ የፈጣሪያችን ውድ ስጦታዎች ናቸው። እሱ በቤተሰብ ሕይወታችን እንድንደሰት ይፈልጋል። ጥንት ባስጻፈው ቅዱስ መጽሐፍ አማካኝነት፣ የቤተሰብ ሕይወት ሰላማዊና አስደሳች እንዲሆን የሚረዳ መመሪያ ሰጥቶናል። እስቲ የሚከተሉትን ጥበብ ያዘሉ ምክሮች ተመልከት።

ባሎች፣ ሚስቶቻችሁን ውደዱ

“ባሎች ሚስቶቻቸውን እንደ ገዛ አካላቸው አድርገው ሊወዷቸው ይገባል። ሚስቱን የሚወድ ሰው ራሱን ይወዳል፤ የገዛ አካሉን የሚጠላ ማንም ሰው የለምና፤ ከዚህ ይልቅ ይመግበዋል እንዲሁም ይሳሳለታል።”—ኤፌሶን 5:28, 29

ባል የቤተሰቡ ራስ ነው። (ኤፌሶን 5:23) ሆኖም ጥሩ ባል ኃይለኛ ወይም አምባገነን አይደለም። ሚስቱን ከልብ ይወዳታል፤ የሚያስፈልጓትን ነገሮች ሁሉ ያቀርባል እንዲሁም እንደምትወደድ እንዲሰማት ያደርጋል። በተጨማሪም እሷን የሚያስደስታትን ነገር ለማድረግ የቻለውን ሁሉ ያደርጋል፤ ሁልጊዜ እኔ ያልኩት ብቻ ካልሆነ አይልም። (ፊልጵስዩስ 2:4) ሐሳቡን በግልጽ ይነግራታል፤ እሷ ስትናገርም በደንብ ያዳምጣታል። “መራራ ቁጣ” አይቆጣትም፤ እንዲሁም አይመታትም ወይም አይሰድባትም።—ቆላስይስ 3:19

ሚስቶች፣ ባሎቻችሁን አክብሩ

“ሚስት ባሏን በጥልቅ ታክብር።”—ኤፌሶን 5:33

አንዲት ሚስት፣ ባሏን የምታከብረውና የሚያደርገውን ውሳኔ የምትደግፍ ከሆነ ለቤተሰቡ ሰላም ትልቅ አስተዋጽኦ ታደርጋለች። ስህተት ቢሠራ እንኳ አታቃልለውም፤ ከዚህ ይልቅ ጉዳዩን በሰከነ መንፈስና በአክብሮት ለመያዝ ጥረት ታደርጋለች። (1 ጴጥሮስ 3:4) ልትነግረው ያሰበችው አንድ ችግር ካለም፣ ይህን የምታደርገው ተስማሚ ጊዜ መርጣ ነው፤ የምታነጋግረውም በአክብሮት ነው።—መክብብ 3:7

ለትዳር ጓደኛችሁ ታማኞች ሁኑ

‘ሰው ከሚስቱ ጋር ይጣበቃል። ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ።’—ዘፍጥረት 2:24

አንድ ወንድና አንዲት ሴት ሲጋቡ በመካከላቸው የጠበቀ ዝምድና ይፈጠራል። ይህ ዝምድና ጠንካራ ሆኖ እንዲቀጥል ባለትዳሮቹ ሁልጊዜ ጥረት ማድረግ አለባቸው፤ ለዚህም የልባቸውን አውጥተው መነጋገራቸውና አንዳቸው ለሌላው ያላቸውን ፍቅር የሚገልጹ ትናንሽ ነገሮች ማድረጋቸው ይጠቅማቸዋል። ከትዳር ጓደኛቸው ውጭ ከማንም ሰው ጋር የፆታ ግንኙነት ባለመፈጸም ለትዳራቸው ታማኝ መሆንም አለባቸው። በትዳር ጓደኛ ላይ መማገጥ ከባድ በደል ነው። በመካከላቸው ያለው መተማመን እንዲጠፋ ያደርጋል እንዲሁም ቤተሰብ ሊያፈርስ ይችላል።—ዕብራውያን 13:4

ወላጆች፣ ልጆቻችሁን ኮትኩታችሁ አሳድጉ

“ልጅን ሊሄድበት በሚገባው መንገድ አሠልጥነው፤ በሚያረጅበት ጊዜም እንኳ ከዚያ ፈቀቅ አይልም።”—ምሳሌ 22:6

አምላክ ለወላጆች ልጆቻቸውን የማሠልጠን ወይም ኮትኩቶ የማሳደግ ኃላፊነት ሰጥቷቸዋል። ይህም ለልጆቻቸው ጥሩ ሥነ ምግባር ማስተማርንና ጥሩ ምሳሌ መሆንን ይጨምራል። (ዘዳግም 6:6, 7) ልጆች ሲያጠፉ፣ ጥበበኛ የሆነ ወላጅ ስሜቱን ይቆጣጠራል። “ለመስማት የፈጠነ፣ ለመናገር የዘገየና ለቁጣ የዘገየ” ለመሆን ይጥራል። (ያዕቆብ 1:19) ልጁ መቀጣት የሚያስፈልገው ከሆነም እንዲህ ዓይነቱ ወላጅ ቅጣት የሚሰጠው በፍቅር እንጂ በቁጣ አይደለም።

ልጆች፣ ወላጆቻችሁን ታዘዙ

“ልጆች ሆይ፣ . . . ለወላጆቻችሁ ታዘዙ፤ . . . ‘አባትህንና እናትህን አክብር።’”—ኤፌሶን 6:1, 2

ልጆች ወላጆቻቸውን መታዘዝና በጥልቅ ማክበር ይኖርባቸዋል። ልጆች ወላጆቻቸውን ሲያከብሩ ቤት ውስጥ ደስ የሚል መንፈስ እንዲኖር ያደርጋሉ፤ በተጨማሪም ቤተሰቡ ሰላማዊ እንዲሆን ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ። ራሳቸውን ችለው የሚኖሩ ልጆች፣ ወላጆቻቸውን በመጦር ለእነሱ ያላቸውን አክብሮት ማሳየት ይችላሉ። ለምሳሌ ቤታቸውን በመጠገን ሊያግዟቸው፣ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም የገንዘብ ድጋፍ ሊያደርጉላቸው ይችላሉ።—1 ጢሞቴዎስ 5:3, 4