በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ተስፋ የሚሰጡ ትምህርቶች

ተስፋ የሚሰጡ ትምህርቶች

አምላክ በቅርቡ በምድር ላይ አስደሳች ጊዜ እንደሚመጣ ቃል ገብቶልናል። በሰው ልጆች ላይ የሚደርሰውን መከራ ያስወግዳል፤ እንዲሁም የሰው ዘር በምድር ላይ ተደስቶ እንዲኖር ያደርጋል። (መዝሙር 37:11) አምላክ በገባው ቃል ላይ እምነት መጣል የምንችለው ለምንድን ነው? ምክንያቱም “አምላክ እንደ ሰው አይዋሽም።” (ዘኁልቁ 23:19) ፈጣሪያችን ከሚያደርግልን መልካም ነገሮች መካከል እስቲ የተወሰኑትን እንመልከት።

አምላክ ክፉ ሰዎችን ያጠፋል

“ክፉዎች እንደ አረም ቢበቅሉ፣ ክፉ አድራጊዎች ሁሉ ቢያብቡ እንኳ፣ ለዘላለም መጥፋታቸው የማይቀር ነው።”—መዝሙር 92:7

ቀደም ባለው ርዕስ ላይ እንደተመለከትነው፣ የሰዎች ክፋት እየጨመረ ነው። ይህ ሊያስገርመን አይገባም። ደግሞም መጽሐፍ ቅዱስ በ2 ጢሞቴዎስ 3:1-5 ላይ “በመጨረሻዎቹ ቀናት” የሰዎች ክፋት ከወትሮው የባሰ እንደሚሆን ይናገራል። የመጨረሻዎቹ ቀናት የተባለው የምን መጨረሻ ነው? በዚህ ዓለም ላይ የሚኖሩ አምላክን የማይታዘዙ ሰዎች መጨረሻ ነው። በቅርቡ አምላክ፣ መጥፎ አካሄዳቸውን ለማስተካከል ፈቃደኛ ያልሆኑ ሰዎችን ያጠፋል። ከዚያ በኋላ በምድር ላይ እንዲኖሩ የሚፈቀድላቸው አምላክን የሚታዘዙ ጥሩ ሰዎች ብቻ ይሆናሉ። “ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፤ በእሷም ላይ ለዘላለም ይኖራሉ።”—መዝሙር 37:29

አምላክ ሰይጣንን ያጠፋዋል

“ሰላም የሚሰጠው አምላክ በቅርቡ ሰይጣንን . . . ይጨፈልቀዋል።”—ሮም 16:20

ሰይጣንን እና አጋንንቱን ጨምሮ ክፉ አድራጊዎች በሙሉ ይወገዳሉ፤ በዚያን ጊዜ ሰላም በመላው ምድር ላይ ይሰፍናል። ፈጣሪያችን ‘የሚያስፈራችሁ አይኖርም’ በማለት ቃል ገብቶልናል።—ሚክያስ 4:4

አምላክ በሽታንና ሞትን ያስወግዳል

“የአምላክ ድንኳን ከሰዎች ጋር ነው፤ . . . እሱም እንባን ሁሉ ከዓይናቸው ያብሳል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት አይኖርም፤ ሐዘንም ሆነ ጩኸት እንዲሁም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይኖርም።”—ራእይ 21:3, 4

አምላክ በሰይጣን፣ በአዳም፣ በሔዋንና በራሳችን ኃጢአት የተነሳ የደረሰውን ጉዳት ሁሉ ያስተካክላል፤ ይህም ሥቃይና ሕመም እንዲወገድ ያደርጋል። ሌላው ቀርቶ ‘ሞት እንኳ አይኖርም።’ ፈጣሪያቸውን የሚወዱና የሚታዘዙ ሰዎች ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ ያገኛሉ። ይሁንና የሚኖሩት የት ነው?

ፈጣሪያችን ምድርን ገነት ያደርጋታል

“ምድረ በዳውና ደረቁ ምድር ሐሴት ያደርጋል፤ በረሃማው ቦታም ደስ ይለዋል፤ እንደ ሳሮን አበባም ያብባል።”—ኢሳይያስ 35:1

አምላክ ክፉዎችን ሲያስወግድ ምድራችን ትለመልማለች! በሚያማምሩ መናፈሻዎችና የአትክልት ቦታዎች የተሞላች ትሆናለች፤ የተትረፈረፈ ምርትም ትሰጣለች። (መዝሙር 72:16) ውቅያኖሶች፣ ሐይቆችና ወንዞች ንጹሕ እንዲሁም ሕይወት ያላቸው ነገሮች የሚርመሰመሱባቸው ይሆናሉ። “የአካባቢ ብክለት” የሚለው አባባል እንኳ የተረሳ ይሆናል! ሰዎች ራሳቸው በሠሩት ቤት ውስጥ ይኖራሉ። ከዚያ በኋላ ቤት አጥቶ ጎዳና ላይ የሚያድር፣ ረሃብተኛ ወይም ድሃ አይኖርም።—ኢሳይያስ 65:21, 22

አምላክ የሞቱ ሰዎችን ያስነሳል

“ሰዎች . . . ከሞት እንደሚነሱ በአምላክ ተስፋ አለኝ።”—የሐዋርያት ሥራ 24:15

በሞት የተለዩህን የምትወዳቸውን ሰዎች እንደገና ማግኘት ትፈልጋለህ? ሁሉን ቻይ የሆነው አምላክ ከሞት ያስነሳቸዋል፤ ገነት በምትሆነው ምድር ላይ እንዲኖሩም ያደርጋል። ከሞት በሚነሱበት ወቅት ማንነታቸውን ማወቅ አትቸገርም፤ እነሱም አንተን ያውቁሃል። ያን ጊዜ አንተም ሆንክ እነሱ ምን ያህል እንደምትደሰቱ አስበው! ይህ ተስፋ እንደሚፈጸም እርግጠኛ የምንሆነው ለምንድን ነው? ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሞት ተነስተው ከቤተሰባቸው ጋር እንደገና ስለተገናኙ አዋቂዎችና ልጆች የሚገልጹ ታሪኮች እናገኛለን። ከዚህም ሌላ ኢየሱስ ሰዎችን ከሞት ሲያስነሳ በአብዛኛው የዓይን ምሥክሮች በቦታው ነበሩ።—ሉቃስ 8:49-56፤ ዮሐንስ 11:11-14, 38-44