በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

“ተላላ ቃልን ሁሉ ያምናል”

“ተላላ ቃልን ሁሉ ያምናል”

“ከናካቴው ጋዜጣ የማያነብ ሰው ሞኝ ነው፤ ጋዜጣ ላይ ስለወጣ ብቻ ያነበበውን ሁሉ የሚያምን ሰው ደግሞ ከዚያ የባሰ ሞኝ ነው።”—አውጉስት ፎን ሽኡትጸ፣ ጀርመናዊ የታሪክ ምሁርና ጋዜጠኛ (1735-1809)

ከ200 ዓመት በፊት አንድ ሰው ጋዜጣ ላይ ያነበበውን ሁሉ ለማመን የሚቸገር ከሆነ በ21ኛው መቶ ዘመን በኢንተርኔት ላይ የሚወጣውን አብዛኛውን ነገር ማመንማ የማይመስል ነገር ነው። ዕድሜ ለቴክኖሎጂ በዛሬው ጊዜ ትክክለኛም ሆነ የተሳሳተ፣ የሚጠቅምም ሆነ የማይጠቅም፣ ጉዳት የማያስከትልም ሆነ ጎጂ የሆነ መረጃ እንደ ልብ ማግኘት ይቻላል። በመሆኑም ትኩረት ልንሰጠው የሚገባውን መረጃ በተመለከተ መራጭ መሆን ይኖርብናል። በተለይ በቅርቡ ኢንተርኔት መጠቀም የጀመሩ ሰዎች አንድ ሪፖርት ወይም ዜና ምንም ያህል አስገራሚ ወይም አስደናቂ ሊሆን ቢችልም ኢንተርኔት ላይ ስለወጣ ወይም ጓደኛቸው በኢሜይል ስለላከላቸው ብቻ እውነት ነው ብለው ማመን አይኖርባቸውም። መጽሐፍ ቅዱስ “ተላላ ቃልን ሁሉ ያምናል፤ ብልህ ግን አካሄዱን አንድ በአንድ ያጤናል” የሚል ማስጠንቀቂያ የሚሰጠው ያለምክንያት አይደለም።—ምሳሌ 14:15

“ብልህ” በመሆን በኢንተርኔት የሚሰራጩ ማጭበርበሪያዎችን፣ ከተማ ውስጥ የሚናፈሱ አሉባልታዎችን፣ ማታለያዎችንና የተዛቡ መረጃዎችን መለየት የምንችለው እንዴት ነው? በመጀመሪያ ራስህን እንዲህ ብለህ ጠይቅ፦ ‘የመረጃው ምንጭ እውቅና ያለውና እምነት የሚጣልበት ድረ ገጽ ነው? ወይስ ከአንድ ብሎግ የተገኘ ነው? ምንጩስ ይታወቃል? ከዚህ በፊት የማጭበርበሪያ መልእክቶችን በሚያጋልጡ ድረ ገጾች ተይዞ ያውቃል?’ * በመሆኑም ጉዳዩን ‘በማስተዋል’ ገምግም። (ምሳሌ 7:7) አንድ ዜና ለማመን የሚያዳግት ከሆነ ውሸት የመሆን አጋጣሚው ሰፊ ነው። በተጨማሪም መረጃው የሌሎችን ስም የሚያጎድፍ ከሆነ የዜናው መሰራጨት ማንን ሊጠቅም እንደሚችል እንዲሁም ምንጩ፣ ዜናው እንዲሰራጭ የፈለገበት ስውር ዓላማ ይኑረው አይኑረው ለማጤን ሞክር።

ለሌሎች የመላክ ሱስ የተጠናወታቸው

አንዳንድ ሰዎች አብዛኛውን ጊዜ የሌሎችን ትኩረት ለማግኘት ሲሉ የደረሳቸውን ወሬ ከሌሎች ቀድመው የማሰራጨት አባዜ የተጠናወታቸው ከመሆኑም ሌላ የወሬውን እውነተኝነት ወይም የሚያስከትለውን መዘዝ ሳያጣሩ ለሚያውቁት ሰው ሁሉ በአድራሻቸው ይልካሉ። (2 ሳሙ. 13:28-33) ይሁን እንጂ “ብልህ” ከሆን እንዲህ ማድረጋችን በአንድ ግለሰብ ወይም ድርጅት ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ጉዳት ቆም ብለን እናስባለን።

የምንሰማውን ዜና ይዘት ማጣራት ጥረት እንደሚጠይቅ የታወቀ ነው። አንዳንዶች የዜናውን ተአማኒነት ሰሚው ራሱ እንዲያጣራ መተው የሚመርጡት ከዚህ የተነሳ ነው። ይሁንና ግለሰቡ እንዲህ ለማድረግ ምን ያህል ጊዜ ሊፈጅበት ይችላል? ጊዜ በዋጋ ሊተመን አይችልም። (ኤፌ. 5:15, 16) “ካመነታህ ላከው” የሚል አመለካከት ከመያዝ ይልቅ “ካመነታህ ተወው!” የሚለውን መርሕ መከተሉ የተሻለ ነው።

ራስህን እንዲህ ብለህ ጠይቅ፦ ‘የደረሰኝን ኢሜይል ሁሉ የመላክ ሱስ ተጠናውቶኛል? የላክሁት መረጃ የተሳሳተ ወይም ያፈጠጠ ውሸት ሆኖ በመገኘቱ ለላክሁላቸው ሰዎች ይቅርታ ለመጠየቅ የተገደድኩበት ጊዜ አለ? የደረሰኝን ኢሜይል ሁሉ እንዳልክለት የጠየቀኝ ሰው አለ?’ በአድራሻቸው ኢሜይል የምትልክላቸው ሰዎች እነሱም ኢንተርኔት መጠቀም ስለሚችሉ ያላንተ እርዳታ የሚፈልጉትን መረጃ የማግኘት አጋጣሚ እንዳላቸው አስታውስ። ቀልዶችን፣ ቪዲዮ ክሊፖችን ወይም ፎቶግራፎችን በብዛት በመላክ ልታጨናንቃቸው አይገባም። ከዚህም ሌላ የመጽሐፍ ቅዱስ ንግግሮችን ቀድተህ ወይም ማስታወሻ ይዘህ ከሆነ ይህን ለሌሎች መላክህ ጥበብ አይደለም። * በተጨማሪም ምርምር አድርገህ ያገኘሃቸውን መረጃዎች፣ ለመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚጠቅሙ ጥቅሶችን ወይም በጉባኤ ስብሰባዎች ላይ የሚሰጡ መልሶችን ለሌሎች መላክህ አንድ ሰው ራሱ ምርምር እንዳያደርግ ሊያሳንፈው ይችላል።

ቆይ እስቲ . . . ይህን የሚያጓጓ ኢሜይል ልላክ?

ኢንተርኔት ላይ የይሖዋን ድርጅት ስም የሚያጎድፍ ዜና ብታገኝስ ምን ማድረግ ይኖርብሃል? እንዲህ ዓይነቱን መረጃ ሙሉ በሙሉ ማስወገድ ይኖርብሃል። አንዳንዶች፣ ሌሎች ወንድሞች ስለ ጉዳዩ የሚሰጡትን አስተያየት ለመስማት ሲሉ ለእነሱ ማሳወቅ እንዳለባቸው ይሰማቸዋል፤ እንዲህ ማድረግ ግን ይህን ጎጂ መረጃ ከማዛመት ሌላ የሚፈይደው ነገር የለም። ኢንተርኔት ላይ ያየነው ነገር ከረበሸን ይሖዋ ጥበብ እንዲሰጠን መጠየቅ እንዲሁም የጎለመሱ ወንድሞችን ማነጋገር ይኖርብናል። (ያዕ. 1:5, 6፤ ይሁዳ 22, 23) ብዙ ጊዜ የሐሰት ክስ ይሰነዘርበት የነበረው ኢየሱስ ተከታዮቹን የሚጠሏቸው ሰዎች እንደሚያሳድዷቸውና ‘ክፉውን ሁሉ በውሸት እንደሚያስወሩባቸው’ አስጠንቅቋቸዋል። (ማቴ. 5:11፤ 11:19፤ ዮሐ. 10:19-21) “ጠማማ ነገር ከሚናገር ሰው” እንዲሁም “አካሄዳቸው በተንኮል ከተሞላ ሰዎች” መራቅ እንድንችል “የማመዛዘን ችሎታ” መጠቀምና “ጥልቅ ግንዛቤ” ማዳበር ያስፈልገናል።—ምሳሌ 2:10-16

የሌሎችን መብት አክብር

አንድ ወንድም ‘የሰማሁት ነው’ ብሎ የሚነግረንን መንፈሳዊ ይዘት ያለውን መረጃ ወይም ተሞክሮ በተመለከተም ጠንቃቆች መሆን አለብን። የሰማነው ወሬ እውነት ቢሆንም እንኳ ለሌሎች የግድ ማዳረስ አለብን ማለት አይደለም። ትክክለኛ ዘገባዎችን ለሌሎች ማዳረስ ተገቢም ሆነ ፍቅራዊ የማይሆንበት ጊዜ ሊኖር ይችላል። (ማቴ. 7:12) ለምሳሌ ያህል፣ የሰማነው ነገር ትክክል ቢሆንም እንኳ ሐሜት መንዛት ፍቅራዊ አይደለም፤ ሌሎችንም አያንጽም። (2 ተሰ. 3:11፤ 1 ጢሞ. 5:13) አንዳንድ ወሬዎች በሚስጥር መያዝ ያለባቸው ከመሆኑም ሌላ ባለጉዳዮቹ መረጃውን በትክክለኛው ጊዜና በተገቢው መስመር ለሌሎች በይፋ ለማሳወቅ ያላቸውን መብት ማክበር ይኖርብናል። ጊዜው ሳይደርስ አንድ መረጃ አፈትልኮ እንዲወጣ ማድረግ ከፍተኛ ጉዳት ሊያስከትል ይችላል።

በዛሬው ጊዜ ማንኛውም ወሬ ትክክለኛም ሆነ የተሳሳተ፣ የሚጠቅምም ሆነ የማይጠቅም፣ ጉዳት የማያስከትልም ሆነ ጎጂ፣ ለመገመት በሚያዳግት ፍጥነት ሊዛመት ይችላል። ማንኛውም ሰው ሆን ብሎም ይሁን በስህተት የኢሜይል ወይም የጽሑፍ መልእክት ለሌላ ግለሰብ ቢልክ የላከው መልእክት በሴኮንድ ውስጥ በመላው ዓለም ሊዳረስ እንደሚችል መገንዘብ ይኖርበታል። በመሆኑም ያገኘነውን መረጃ ቸኩለንና ሳናመዛዝን ለሌሎች ለማስተላለፍ በሚያድርብን ጉጉት ላለመሸነፍ እንጠንቀቅ። ለመስማት የሚያጓጓ ወሬ ሲደርሰን ፍቅር፣ አንድም ከልክ በላይ ተጠራጣሪ አለመሆኑን ሌላም ተላላ ወይም ሞኛሞኝ አለመሆኑን እናስታውስ። ከሁሉም በላይ ፍቅር፣ “የውሸት አባት” የሆነው የሰይጣን ዲያብሎስ ባሪያ የሆኑ ሰዎች ስለ ይሖዋ ድርጅት በረቀቀ መንገድ የሚያወሩትን የተዛባ ወሬ ወይም ስለ ወንድሞቻችን የሚያዛምቱትን ውሸት ከማመን እንድንርቅ ይረዳናል። (ዮሐ. 8:44፤ 1 ቆሮ. 13:7) የማመዛዘን ችሎታና ጥልቅ ግንዛቤ “ብልህ” እንድንሆን የሚረዳን ከመሆኑም ሌላ በየቀኑ የምናገኘውን ብዛት ያለው መረጃ ኃላፊነት እንደሚሰማን በሚያሳይ መንገድ እንዴት ልንጠቀምበት እንደሚገባ እንድናጤን ይረዳናል። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለው “ተላሎች ሞኝነትን ይወርሳሉ፤ ብልሆች ግን እውቀትን እንደ አክሊል ይጎናጸፋሉ።”—ምሳሌ 14:18

^ አን.4 ከዚህ ቀደም የተያዙ ማጭበርበሪያዎችና አሉባልታዎች እንደገና ሊናፈሱ፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በመጠኑ ተሻሽለው እውነት መስለው ሊቀርቡ ስለሚችሉ እንዳትታለል ተጠንቀቅ።

^ አን.8 የሚያዝያ 2010 የመንግሥት አገልግሎታችን የጥያቄ ሣጥን” ተመልከት።