በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

 ንድፍ አውጪ አለው?

የእባብ ቆዳ

የእባብ ቆዳ

እባቦች እግር ስለሌላቸው በደረታቸው እየተሳቡ በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ መፋተግ ይፈጠራል፤ በመሆኑም ይህንን መቋቋም የሚችል ጠንካራ ቆዳ ያስፈልጋቸዋል። አንዳንዶቹ የእባብ ዝርያዎች ሸካራ ቅርፊት ባለው የዛፍ ግንድ ላይ ይወጣሉ፤ ሌሎቹ ደግሞ ቆዳን በሚፈትግ አሸዋ ውስጥ ሰርስረው ይገባሉ። የእባብ ቆዳ ይህን ያህል ጠንካራ እንዲሆን ያደረገው ምንድን ነው?

እስቲ የሚከተለውን አስብ፦ የእባብ ቆዳ ውፍረቱም ሆነ አሠራሩ ከአንዱ ዝርያ ወደ ሌላው ሊለያይ ይችላል። ይሁን እንጂ የሁሉም የእባብ ዝርያዎች ቆዳ አንድ የጋራ ባሕርይ አለው፤ ውጩ ድርቅ ያለ ሲሆን ወደ ውስጥ እየገባ ሲሄድ ለስላሳ ይሆናል። ይህ ጠቃሚ የሆነው ለምንድን ነው? ማሪ ክርስቲን ክላይን የተባሉ ተመራማሪ እንዲህ ብለዋል፦ “ውጫቸው ድርቅ ያለ ሆኖ ውስጣቸው እየለሰለሱ የሚሄዱ ነገሮች፣ የሚወጋ ወይም የሚጫን ነገር ሲያጋጥማቸው ግፊቱ ወደተለያዩ አቅጣጫዎች እንዲሰበጣጠር ማድረግ ይችላሉ።” በልዩ መንገድ የተሠራው የእባብ ቆዳ፣ ሰውነቱ መሬቱን በደንብ እንዲቆነጥጥ በማድረግ እንደ ልብ እንዲንቀሳቀስ ያስችለዋል፤ እንዲሁም እንደ ሹል ድንጋይ ያሉ ነገሮች ሰውነቱ ላይ የሚያደርሱት ግፊት እንዲበተን በማድረግ ቆዳው ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ይከላከላል። እባቦች ቆዳቸውን የሚቀይሩት በየሁለት ወይም በየሦስት ወር በመሆኑ ጠንካራ መሆኑ በጣም አስፈላጊ ነው።

ከእባብ ቆዳ ጋር የሚመሳሰል ባሕርይ ያላቸው ነገሮች በሕክምናው መስክ ጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ፤ ለምሳሌ፣ የማይንሸራተቱና ልዩ ጥንካሬ ያላቸው ሰው ሠራሽ አካሎችን ለመሥራት ያገለግላሉ። በተጨማሪም የእባብ ቆዳን ንድፍ በመኮረጅ የሚሠሩ ባለቺንግያ የዕቃ ማጓጓዣ ኮንቬየሮች የሚፈልጉት ማለስለሻ ቅባት አነስተኛ ነው፤ ይህ ደግሞ እነዚህ ቅባቶች የሚያስከትሉት ብክለት እንዲቀንስ ያደርጋል።

ታዲያ ምን ይመስልሃል? የእባብ ቆዳ በዝግመተ ለውጥ የተገኘ ነው? ወይስ ንድፍ አውጪ አለው?