በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ትምህርት 6

የሥነ ምግባር እሴቶች አስፈላጊነት

የሥነ ምግባር እሴቶች አስፈላጊነት

የሥነ ምግባር እሴቶች ምንድን ናቸው?

በሥነ ምግባር እሴቶች የሚመሩ ሰዎች ትክክልና ስህተት ስለሆኑት ነገሮች ጥርት ያለ ግንዛቤ አላቸው። ትክክል ወይም ስህተት የሆነውን ነገር የሚወስኑት በወቅቱ በተሰማቸው ስሜት ላይ ተመሥርተው አይደለም። ከዚህ ይልቅ ምን ዓይነት ምግባር ማሳየት እንዳለባቸው የሚወስኑት ጠንካራ መሠረት ባላቸው የሥነ ምግባር እሴቶች ላይ ተመሥርተው ነው፤ ደግሞም ሰው አያቸውም አላያቸው አቋማቸውን አይቀያይሩም።

የሥነ ምግባር እሴቶች አስፈላጊ የሆኑት ለምንድን ነው?

ልጆች ትክክልና ስህተት የሆኑትን ነገሮች በተመለከተ ብዙ የተዛቡ መረጃዎች ይደርሷቸዋል፤ አብረዋቸው የሚማሩ ልጆች፣ የሚያዳምጡት ሙዚቃ ወይም የሚመለከቷቸው ፊልሞችና የቴሌቪዥን ፕሮግራሞች ተገቢ ከሆነው ምግባር ጋር በተያያዘ የተሳሳተ መልእክት ያስተላልፋሉ። እንዲህ ያሉት ተጽዕኖዎች ልጆች ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር በተመለከተ ግራ እንዲጋቡ ሊያደርጉ ይችላሉ።

በተለይ በአሥራዎቹ የዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ልጆች እንዲህ ያለ ችግር ያጋጥማቸዋል። ቢዮንድ ዘ ቢግ ቶክ የተባለው መጽሐፍ እንደሚናገረው፣ በዚህ ዕድሜ ላይ የሚገኙ ልጆች “መገናኛ ብዙኃንም ሆነ እኩዮቻቸው በሌሎች ዘንድ ተቀባይነት እንዲያገኙ ከፍተኛ ተጽዕኖ እንደሚያሳድሩባቸው መረዳት አለባቸው፤ በተጨማሪም ከጓደኞቻቸው ተቃራኒ የሆነ ነገር ማድረግ የሚጠይቅባቸው ቢሆንም እንኳ በራሳቸው የሥነ ምግባር እሴቶችና ምርጫዎች ላይ ተመሥርተው ውሳኔ ማድረግን መማር ያስፈልጋቸዋል።” በግልጽ ማየት እንደሚቻለው፣ ወላጆች ሥልጠናውን መጀመር ያለባቸው ከጉርምስና ዕድሜ በፊት ነው።

የሥነ ምግባር እሴቶችን ማስተማር የሚቻለው እንዴት ነው?

ትክክልና ስህተት ስለሆነው ነገር በግልጽ አስተምሯቸው።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ጠንካራ ምግብ . . . ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር መለየት እንዲችሉ የማስተዋል ችሎታቸውን በማሠራት ላሠለጠኑ ጎልማሳ ሰዎች ነው።”—ዕብራውያን 5:14

  • ትክክልና ስህተት የሆኑትን ነገሮች ለይተው የሚያስቀምጡ አገላለጾችን ተጠቀሙ። በዕለት ተዕለት የሚያጋጥሙ ሁኔታዎችን በማንሳት በንጽጽር ንገሯቸው፦ “ይህ ሐቀኝነት ነው፤ ይህ ደግሞ ሐቀኝነት የጎደለው ነገር ነው።” “ይህ ታማኝነት ነው፤ ይህ ደግሞ ታማኝነትን ማጉደል ነው።” “ይህ ደግነት ነው፤ ይህ ደግሞ ደግነት የጎደለው ነገር ነው።” በጊዜ ሂደት ልጃችሁ ተገቢ የሆነው ምግባር የቱ እንደሆነ ተገንዝቦ በዚያ መመራት ይጀምራል።

  • አንድን ነገር ትክክል ወይም ስህተት ነው የምትሉበትን ምክንያት አስረዷቸው። ለምሳሌ ያህል፣ ‘ሐቀኛ መሆን ምንጊዜም የተሻለ ነው የምንለው ለምንድን ነው? መዋሸት ጓደኝነትን ሊያበላሽ የሚችለው እንዴት ነው? መስረቅ ስህተት የሆነው ለምንድን ነው?’ እንደሚሉት ያሉ ጥያቄዎችን ጠይቁ። ልጃችሁ ሕሊናውንና የማመዛዘን ችሎታውን እንዲጠቀም በሚያደርግ መንገድ አስረዱት።

  • ጥሩ በሆኑ የሥነ ምግባር እሴቶች መመራት ያሉትን ጥቅሞች ጎላ አድርጋችሁ ግለጹ። ለምሳሌ ልጃችሁን “ሐቀኛ ከሆንክ ሰዎች ያምኑሃል” ወይም “ደግ ከሆንክ ሰዎች ከአንተ ጋር መሆን ደስ ይላቸዋል” ልትሉት ትችላላችሁ።

እናንተ የምትመሩባቸው የሥነ ምግባር እሴቶች የቤተሰባችሁ መለያ እንዲሆኑ አድርጉ።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ማንነታችሁን ለማወቅ ዘወትር ራሳችሁን መርምሩ።”—2 ቆሮንቶስ 13:5

  • መላው ቤተሰባችሁ እናንተ በምትመሩባቸው የሥነ ምግባር እሴቶች ሊመራ ይገባል፤ ይህ ከሆነ አፋችሁን ሞልታችሁ እንዲህ ማለት ትችላላችሁ፦

    • “የእኛ ቤተሰብ አይዋሽም።”

    • “ሰዎችን አንማታም ወይም በሌሎች ላይ አንጮህም።”

    • “በቤተሰባችን ውስጥ ስድብ ፈጽሞ አይፈቀድም።”

ልጃችሁ፣ የሚማራቸው የሥነ ምግባር እሴቶች እንዲሁ ሕጎች ሳይሆኑ የቤተሰባችሁ መለያ ምልክት እንደሆኑ ሊያይ ይገባል።

  • ቤተሰባችሁ ስለሚመራባቸው የሥነ ምግባር እሴቶች አዘውትራችሁ ከልጃችሁ ጋር ተወያዩ። በዕለት ተዕለት የሚያጋጥሙ ሁኔታዎችን ልጃችሁን ለማስተማር ተጠቀሙባቸው። የእናንተን የሥነ ምግባር እሴቶች በቴሌቪዥን ላይ ከሚቀርቡት ወይም ልጃችሁ በትምህርት ቤት ከሚሰማቸው የሥነ ምግባር እሴቶች ጋር ልታነጻጽሩለት ትችላላችሁ። ልጃችሁን “አንተ ብትሆን ኖሮ ምን ታደርግ ነበር? ቤተሰባችን እንዲህ ዓይነት ሁኔታ ቢያጋጥመው ምን የሚያደርግ ይመስልሃል?” እንደሚሉት ያሉ ጥያቄዎችን ጠይቁት።

ልጆቻችሁ ትክክል የሆነውን ነገር ለማድረግ ያላቸውን ቁርጠኝነት አጠናክሩ።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ጥሩ ሕሊና ይኑራችሁ።”—1 ጴጥሮስ 3:16

  • ልጃችሁን ላሳየው ጥሩ ምግባር አመስግኑት። ልጃችሁ ጥሩ ሥነ ምግባር እንዳለው የሚያሳይ ነገር በሚያደርግበት ጊዜ አመስግኑት፤ ለምን እንዳመሰገናችሁትም ግለጹለት። ለምሳሌ “ሐቀኛ በመሆንህ በጣም ኮርቼብሃለሁ” ልትሉት ትችላላችሁ። ልጃችሁ አንድ ስህተት እንደሠራ ከነገራችሁ እርማት ከመስጠታችሁ በፊት ስለ ሐቀኝነቱ ከልብ አመስግኑት።

  • መጥፎ ምግባር ሲያሳይ እርማት ስጡት። ልጃችሁ ለፈጸመው ድርጊት ኃላፊነት እንዲወስድ አድርጉ። ልጆች፣ ያደረጉት ነገር ስህተት የሆነው ለምን እንደሆነና ከቤተሰቡ የሥነ ምግባር መመሪያ ጋር የሚቃረነው እንዴት እንደሆነ ማወቅ አለባቸው። አንዳንድ ወላጆች ልጆቻቸውን ቅር እንዳያሰኙ ስለሚፈሩ ለልጆቻቸው ጥፋታቸውን ከመንገር ወደኋላ ይላሉ፤ ሆኖም ልጆች ጥፋታቸው ምን እንደሆነ ማወቃቸው ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር መለየት የሚችል ጥሩ ሕሊና እንዲያዳብሩ ይረዳቸዋል።