በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ከሙት ባሕር ጥቅልሎች ላይ የተወሰደ የኢሳይያስ መጽሐፍ የተወሰነ ክፍል፤ ከታች ያለው በዘመናችን በተዘጋጀ የአረብኛ ትርጉም ላይ የሚገኝ የኢሳይያስ መጽሐፍ ክፍል ነው። በአምላክ ቃል ውስጥ የሚገኘው መልእክት አልተቀየረም

በጽሑፍ የሰፈረው የአምላክ ቃል ተቀይሯል?

በጽሑፍ የሰፈረው የአምላክ ቃል ተቀይሯል?

አንዳንድ ሰዎች በጽሑፍ የሰፈረው የአምላክ ቃል እንደተቀየረ ይሰማቸዋል። ሆኖም ነቢዩ ኢሳይያስ፣ የአምላክ ቃል “ለዘላለም ጸንቶ ይኖራል” በማለት ተናግሯል። (ኢሳይያስ 40:8) ታዲያ የአምላክ ቃል በትክክል ተጠብቆ እንደቆየ እርግጠኛ እንድንሆን የሚያደርገን ምንድን ነው?

አምላክ፣ ቃሉ ሳይለወጥ ተጠብቆ እንዲቆይ እንዲሁም መልእክቱ እንዳይበረዝ ለማድረግ የሚያስችል ኃይል አለው። ጥንት ቅዱሳን መጻሕፍት በእጅ ይገለበጡ በነበረበት ወቅት፣ ጠንቃቃ የሆኑት ገልባጮች እያንዳንዱን ፊደል ይቆጥሩ ነበር፤ ይህን የሚያደርጉት በሚገለብጡበት ወቅት የጨመሩት፣ የቀየሩት ወይም ያስቀሩት ነገር አለመኖሩን ለማረጋገጥ ነው። ያም ቢሆን ከሰው ስህተት ስለማይጠፋ አንዳንድ ገልባጮች ጥቃቅን ስህተቶችን ሠርተዋል።

በዛሬው ጊዜ ያሉት ቅዱሳን መጻሕፍት አምላክ መጀመሪያ ያስጻፈውን መልእክት እንደያዙ እንዴት እርግጠኛ መሆን እንችላለን?

በዛሬው ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ጥንታዊ የቅዱሳን መጻሕፍት ቅጂዎች አሉ። በአንዱ ቅጂ ላይ ትንሽ ስህተት እንኳ ቢገኝ ከሌሎች ቅጂዎች ጋር በማነጻጸር ትክክለኛውን ሐሳብ ማወቅ ይቻላል።—ስለዚህ ጉዳይ ተጨማሪ ሐሳብ ለማግኘት jw.org ላይ የሚገኘውን “የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ተቀይሯል ወይም ተበርዟል?” የሚለውን ርዕስ ተመልከት።

የሙት ባሕር ጥቅልሎች ተብለው የሚጠሩትን ጥንታዊ ሰነዶች እንደ ምሳሌ እንውሰድ፤ በ1947 በሙት ባሕር አቅራቢያ ባሉ ዋሻዎች ውስጥ እነዚህን ጥቅልሎች ያገኟቸው አረቦች ናቸው። እነዚህ ጥንታዊ ሰነዶች፣ ከሁለት ሺህ ከሚበልጡ ዓመታት በፊት የተጻፉ የቅዱሳን መጻሕፍት ክፍሎችን ይዘዋል። ምሁራን እነዚህን ጥንታዊ ቅጂዎች አሁን ካሉት ቅዱሳን መጻሕፍት ጋር አነጻጽረዋቸዋል። ታዲያ ውጤቱ ምን ሆነ?

ምሁራን በዛሬው ጊዜ ባለው የአምላክ ቃል ውስጥ የሰፈረው ሐሳብ በጥንታዊ ቅጂዎች ውስጥ ከሚገኘው ሐሳብ ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ አረጋግጠዋል። * ጥንታዊ ቅጂዎችን በጥንቃቄ በመመርመር የተገኘው ውጤት፣ ዛሬ በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ የሚገኘው ሐሳብ አምላክ መጀመሪያ ካስጻፈው መልእክት ጋር ተመሳሳይ እንደሆነ አሳይቷል። አምላክ በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ ያሰፈረልን መልእክት ሳይቀየር እስከ ዘመናችን እንዲደርስ በሚገባ እንደጠበቀው እርግጠኞች መሆን እንችላለን።

በመሆኑም የአምላክ ቃል የያዘው መልእክት ትክክለኛ እንደሆነ ሙሉ በሙሉ መተማመን እንችላለን። ይህን በአእምሯችን ይዘን፣ ነቢያት ስለ አምላክ ከተናገሩት ነገር ምን እንደምንማር እስቲ እንመልከት።

^ አን.7 በጌዛ ቨርምስ የተዘጋጀው ዘ ኮምፕሊት ዴድ ሲ ስክሮልስ ኢን ኢንግሊሽ፣ ገጽ 16