የማቴዎስ ወንጌል 10:1-42
10 ከዚያም ኢየሱስ 12ቱን ደቀ መዛሙርት ጠርቶ ርኩሳን መናፍስትን እንዲያዝዙ ሥልጣን ሰጣቸው፤+ ይህን ያደረገውም ርኩሳን መናፍስትን እንዲያስወጡ እንዲሁም ማንኛውንም ዓይነት በሽታና ማንኛውንም ዓይነት ሕመም እንዲፈውሱ ነው።
2 የ12ቱ ሐዋርያት ስም የሚከተለው ነው፦+ በመጀመሪያ፣ ጴጥሮስ የተባለው ስምዖንና+ ወንድሙ እንድርያስ፣+ የዘብዴዎስ ልጅ ያዕቆብና ወንድሙ ዮሐንስ፣+
3 ፊልጶስና በርቶሎሜዎስ፣+ ቶማስና+ ቀረጥ ሰብሳቢው ማቴዎስ፣+ የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብና ታዴዎስ፣
4 ቀነናዊው* ስምዖንና በኋላ ኢየሱስን የከዳው የአስቆሮቱ ይሁዳ።+
5 ኢየሱስ እነዚህን 12ቱን የሚከተለውን መመሪያ በመስጠት ላካቸው፦+ “ወደ አሕዛብ አትሂዱ፤ ወደ ማንኛውም የሳምራውያን ከተማም+ አትግቡ፤
6 ከዚህ ይልቅ ከእስራኤል ቤት ወደጠፉት በጎች ብቻ ሂዱ።+
7 በምትሄዱበት ጊዜም ‘መንግሥተ ሰማያት ቀርቧል’ ብላችሁ ስበኩ።+
8 የታመሙትን ፈውሱ፤+ የሞቱትን አስነሱ፤ የሥጋ ደዌ ያለባቸውን አንጹ፤ አጋንንትንም አስወጡ። በነፃ እንደተቀበላችሁ በነፃ ስጡ።
9 ወርቅ ወይም ብር አሊያም መዳብ በመቀነታችሁ አትያዙ፤+
10 ወይም ለጉዞ የምግብ ከረጢት ወይም ሁለት ልብስ* ወይም ትርፍ ጫማ ወይም በትር አትያዙ፤+ ለሠራተኛ ምግቡ ይገባዋልና።+
11 “በምትገቡበት ማንኛውም ከተማ ወይም መንደር መልእክቱን መስማት የሚገባውን ሰው ፈልጉ፤ እስክትወጡም ድረስ እዚያው ቆዩ።+
12 ወደ ቤትም ስትገቡ ቤተሰቡን ሰላም በሉ።
13 ቤቱ የሚገባው ሆኖ ከተገኘ ሰላማችሁ ይድረሰው፤+ የማይገባው ከሆነ ግን ሰላማችሁ ወደ እናንተ ይመለስ።
14 የሚቀበላችሁ ወይም ቃላችሁን የሚሰማ ሰው ካጣችሁ ከዚያ ቤት ወይም ከተማ ስትወጡ፣ የእግራችሁን አቧራ አራግፉ።*+
15 እውነት እላችኋለሁ፣ በፍርድ ቀን ከዚያች ከተማ ይልቅ ለሰዶምና ለገሞራ+ ይቀልላቸዋል።
16 “እነሆ፣ በተኩላዎች መካከል እንዳሉ በጎች እልካችኋለሁ፤ ስለዚህ እንደ እባብ ጠንቃቆች፣ እንደ ርግብ የዋሆች ሁኑ።+
17 ሰዎች ለፍርድ ሸንጎዎች አሳልፈው ይሰጧችኋል፤+ በምኩራቦቻቸውም+ ይገርፏችኋል፤+ ስለዚህ ራሳችሁን ከእነሱ ጠብቁ።
18 ደግሞም በእኔ ምክንያት በገዢዎችና በነገሥታት ፊት ያቀርቧችኋል፤+ በዚያ ጊዜ ለእነሱም ሆነ ለአሕዛብ መመሥከር ትችላላችሁ።+
19 ይሁን እንጂ አሳልፈው ሲሰጧችሁ እንዴት ወይም ምን ብለን እንመልሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ፤ የምትናገሩት ነገር በዚያኑ ሰዓት ይሰጣችኋልና፤+
20 በምትናገሩበት ጊዜ ብቻችሁን አይደላችሁም፤ ይልቁንም በእናንተ የሚናገረው የአባታችሁ መንፈስ ነው።+
21 በተጨማሪም ወንድም ወንድሙን፣ አባትም ልጁን ለሞት አሳልፎ ይሰጣል፤ ልጆችም በወላጆቻቸው ላይ ይነሳሉ፤ ደግሞም ያስገድሏቸዋል።+
22 በስሜ የተነሳም ሰዎች ሁሉ ይጠሏችኋል፤+ እስከ መጨረሻው የጸና* ግን ይድናል።+
23 በአንድ ከተማ ስደት ሲያደርሱባችሁ ወደ ሌላ ከተማ ሽሹ፤+ እውነት እላችኋለሁ፣ የሰው ልጅ እስከሚመጣ ድረስ የእስራኤልን ከተሞችና መንደሮች ፈጽሞ አታዳርሱም።
24 “ተማሪ* ከአስተማሪው፣ ባሪያም ከጌታው አይበልጥም።+
25 ተማሪ እንደ አስተማሪው፣ ባሪያም እንደ ጌታው ከሆነ በቂ ነው።+ ሰዎች የቤቱን ጌታ ብዔልዜቡል*+ ካሉት ቤተሰቦቹንማ እንዴት ከዚህ የከፋ አይሏቸው!
26 ስለዚህ አትፍሯቸው፤ የተሸፈነ ሁሉ መገለጡ፣ ሚስጥር የሆነም ሁሉ መታወቁ አይቀርም።+
27 በጨለማ የነገርኳችሁን በብርሃን ተናገሩ፤ በሹክሹክታ የሰማችሁትንም በይፋ ስበኩ።+
28 ሥጋን የሚገድሉትን ነፍስን* ግን መግደል የማይችሉትን አትፍሩ፤+ ከዚህ ይልቅ ነፍስንም ሆነ ሥጋን በገሃነም* ሊያጠፋ የሚችለውን ፍሩ።+
29 ሁለት ድንቢጦች የሚሸጡት አነስተኛ ዋጋ ባላት ሳንቲም* አይደለም? ሆኖም ከእነሱ አንዷም እንኳ አባታችሁ ሳያውቅ መሬት ላይ አትወድቅም።+
30 የራሳችሁ ፀጉር እንኳ አንድ ሳይቀር ተቆጥሯል።
31 ስለዚህ አትፍሩ፤ እናንተ ከብዙ ድንቢጦች የላቀ ዋጋ አላችሁ።+
32 “እንግዲያው በሰዎች ፊት ለሚመሠክርልኝ+ ሁሉ እኔም በሰማያት ባለው አባቴ ፊት እመሠክርለታለሁ።+
33 በሰዎች ፊት የሚክደኝን ሁሉ ግን እኔም በሰማያት ባለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ።+
34 በምድር ላይ ሰላም ለማስፈን የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ የመጣሁት ሰይፍን እንጂ ሰላምን ለማምጣት አይደለም።+
35 እኔ የመጣሁት ወንድ ልጅን ከአባቱ፣ ሴት ልጅን ከእናቷ እንዲሁም ምራትን ከአማቷ ለመለያየት ነው።+
36 በእርግጥም የሰው ጠላቶቹ የገዛ ቤተሰቦቹ ይሆናሉ።
37 ከእኔ ይልቅ አባቱን ወይም እናቱን የሚወድ ሁሉ ለእኔ ሊሆን አይገባም፤ ከእኔ ይልቅ ወንድ ልጁን ወይም ሴት ልጁን የሚወድ ሁሉ ለእኔ ሊሆን አይገባም።+
38 የመከራውን እንጨት* የማይቀበልና የማይከተለኝ ሁሉ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።+
39 ነፍሱን* ለማዳን የሚሞክር ሁሉ ያጣታል፤ ነፍሱን* ስለ እኔ አሳልፎ የሚሰጥ ሁሉ ግን ያገኛታል።+
40 “እናንተን የሚቀበል ሁሉ እኔን ይቀበላል፤ እኔን የሚቀበል ሁሉ ደግሞ የላከኝን ይቀበላል።+
41 ነቢይን ስለ ነቢይነቱ የሚቀበል ሁሉ የነቢይን ዋጋ ያገኛል፤+ ጻድቅን ስለ ጻድቅነቱ የሚቀበል ሁሉ የጻድቅን ዋጋ ያገኛል።
42 እውነት እላችኋለሁ፣ የእኔ ደቀ መዝሙር በመሆኑ ምክንያት ከእነዚህ ከትናንሾቹ ለአንዱ አንድ ብርጭቆ ቀዝቃዛ ውኃ የሚሰጥ ሁሉ በምንም ዓይነት ዋጋውን አያጣም።”+
የግርጌ ማስታወሻዎች
^ ወይም “ቀናተኛው።”
^ ወይም “ትርፍ ልብስ።”
^ የእግርን አቧራ ማራገፍ ከኃላፊነት ነፃ መሆንን ያመለክታል።
^ ወይም “የሚጸና።”
^ ወይም “ደቀ መዝሙር።”
^ የአጋንንት አለቃ ወይም ገዢ ለሆነው ለሰይጣን የተሰጠ ስያሜ ነው።
^ ወይም “ሕይወትን።” የወደፊት ሕይወት ተስፋን ያመለክታል።
^ የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
^ የቃላት መፍቻውን ተመልከት።
^ ወይም “ሕይወቱን።”
^ ወይም “ሕይወቱን።”