በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

ጎርፉ ምሥራች አመጣ

ጎርፉ ምሥራች አመጣ

 በ2017 አሥራ ሁለት የይሖዋ ምሥክሮች በኒካራጓ ከሚገኘው የሚስኪቶ የባሕር ዳርቻ ተነስተው በጀልባ መጓዝ ጀመሩ። የጀልባቸው ስም ስቱሪ ያምኒ ነበር። ስቲቨን የተባለ አንድ የቡድኑ አባል እንዲህ ብሏል፦ “ግባችን ርቆ በሚገኝ አካባቢ የሚኖሩ ጥቂት የይሖዋ ምሥክሮችን ማበረታታትና ሰፊ በሆነው የአገልግሎት ክልላቸው ምሥራቹን እንዲያዳርሱ መርዳት ነበር።”

 አሥራ ሁለቱ የይሖዋ ምሥክሮች ከፐርል ላጉን ተነስተው ሪዮ ግራንዴ ዴ ማታጋልፓ የተባለውን ወንዝ በመከተል የ200 ኪሎ ሜትር ጉዞ አደረጉ። በሚስኪቶ ቋንቋ “ምሥራች” የሚል ትርጉም ያለው የጀልባቸው ስም በወንዙ ዳርቻ ለሚኖሩት ሰዎች ልዩ ትርጉም እንደሚኖረው በወቅቱ አላወቁም ነበር። ለአዳር ያረፉበት ጊዜ ሳይቆጠር ለ12 ሰዓት ከተጓዙ በኋላ ወደ ላ ክሩዝ ዴ ሪዮ ግራንዴ ደረሱ። በዚያ ቦታ ያሉት ስድስት የይሖዋ ምሥክሮች ለእነዚህ ወንድሞችና እህቶች ሞቅ ያለ አቀባበል አደረጉላቸው።

 በዚያ ሌሊት አንድ አደጋ ተከሰተ። በሪዮ ግራንዴ ዴ ማታጋልፓ ወንዝ መነሻ አካባቢ ከፍተኛ ዝናብ ጣለ። በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ወንዙ ተጥለቀለቀ፤ ለቀጣዮቹ ሁለት ቀናትም የጎርፉ መጠን መጨመሩን አላቆመም። በላ ክሩዝ የሚገኘው የስብሰባ አዳራሽና ሌሎች በርካታ ቤቶች ተጥለቀለቁ። ለጉብኝት የሄዱት ወንድሞች የአካባቢው ሰዎች መኖሪያቸውን ለቀው እንዲወጡ ረዷቸው። ብዙዎቹ ሰዎች ቀጣዮቹን ሁለት ሌሊቶች ያደሩት ባለአንድ ፎቅ በሆነ የአንዲት እህት ቤት ውስጥ ነበር።

በላ ክሩዝ የሚገኘው የስብሰባ አዳራሽ በጎርፍ ተጥለቅልቆ

 በሦስተኛው ሌሊት የላ ክሩዝ ከንቲባ ወደ ጎብኚዎቹ መጥተው እርዳታቸውን ጠየቁ። በተጥለቀለቀው ወንዝ ላይ የመሄድ አቅም የነበራት ስቱሪ ያምኒ ብቻ በመሆኗ ሌሎቹን መንደሮች ለመርዳት የሚሄዱትን የእርዳታ ሠራተኞች እነዚህ ወንድሞች በጀልባቸው አሳፍረው እንዲወስዷቸው ከንቲባው ጠየቁ። ወንድሞችም ለመተባበር ፈቃደኛ ነበሩ።

 በማግስቱ ጠዋት ሦስት የይሖዋ ምሥክሮች የእርዳታ ሠራተኞቹን አሳፍረው ጉዞ ጀመሩ። ስቲቨን እንዲህ ብሏል፦ “በወቅቱ ወንዙ እየነጎደ ነበር። ጎርፉ የነቀላቸው ትላልቅ ዛፎች ወንዙ ላይ ሲሄዱ ይታዩ ነበር፤ ውኃው ላይም ብዙ ሽክርክሪቶች ተፈጥረው ነበር። ወንዙ በሰዓት 18 ኪሎ ሜትር ይጓዝ ነበር።” እነዚህ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ቢኖሩም ጀልባዋ ወደ ሦስት መንደሮች መድረስ ችላለች።

 ሦስቱ የይሖዋ ምሥክሮች መንደርተኞቹ በእጅጉ የሚያስፈልጋቸውን ማጽናኛ ለመስጠት አጋጣሚውን ተጠቀሙበት። ከዚህም በተጨማሪ “አደጋ ሲደርስ ሕይወት ለማዳን የሚያስችሉ እርምጃዎች” የሚል ትኩረት የሚስብ ርዕስ ያለውን የ2017 ንቁ! አሰራጩ።

 በወንዙ ዳርቻ የሚኖሩት መንደርተኞች ወንድሞች ለሰጧቸው ቁሳዊና መንፈሳዊ እርዳታ ያላቸውን አድናቆት ገልጸዋል። አንዳንድ ሰዎች “በአስቸጋሪ ወቅት እርዳታ ለማበርከት ፈቃደኞች ናቸው” በማለት ተናግረዋል። ሌሎቹ ደግሞ “ለሰዎች እውነተኛ ፍቅር አላቸው” ብለዋል። ብዙዎቹ መንደርተኞች ወንድሞች የእምነት አጋሮቻቸውንም ሆነ ሌሎችን ለመርዳት ያደረጉትን ጥረት ከተመለከቱ በኋላ አጽናኝ የሆነውን የመጽሐፍ ቅዱስ መልእክት ለማዳመጥ ፈቃደኛ ሆነዋል።

ጀልባውን ከሚነዱት ወንድሞች አንዱ የሆነው ማርኮ ከስቱሪ ያምኒ ወጥቶ ለመንደርተኞቹ ምሥራቹን ለመስበክ ሲሄድ

ስቱሪ ያምኒ በጎርፍ በተጥለቀለቀው መንደር ዳርቻ ቆማ