የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው
አምላክ ሁሉንም ጸሎቶች ይሰማል?
አምላክ፣ ከየትኛውም ብሔር ቢሆኑ ሰዎች የሚያቀርቡትን ጸሎት ይሰማል። (መዝሙር 145:18, 19) ስለሚያሳስበን ማንኛውም ጉዳይ እንድንጸልይ ቃሉ መጽሐፍ ቅዱስ ያበረታታናል። (ፊልጵስዩስ 4:6, 7) ሆኖም አንዳንድ ጸሎቶች አምላክን አያስደስቱትም። ለምሳሌ ያህል፣ የተሸመደዱ ጸሎቶችን ደጋግሞ ማቅረብ አምላክን አያስደስተውም።—ማቴዎስ 6:7ን አንብብ።
በተጨማሪም ይሖዋ ሆን ብለው ሕጎቹን ችላ የሚሉ ሰዎች የሚያቀርቧቸውን ጸሎቶች ይጠላል። (ምሳሌ 28:9) ለምሳሌ ያህል፣ በጥንት ዘመን ነፍስ በማጥፋት ተጠያቂ የነበሩት እስራኤላውያን ያቀረቧቸውን ጸሎቶች ለመስማት ፈቃደኛ አልነበረም። ከዚህ በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው ጸሎታችን በአምላክ ዘንድ ተሰሚነት እንዲያገኝ ልናሟላቸው የሚገቡ የተወሰኑ መሥፈርቶች አሉ።—ኢሳይያስ 1:15ን አንብብ።
አምላክ ጸሎታችንን እንዲሰማ ምን ማድረግ ይኖርብናል?
ያለ እምነት ወደ አምላክ በጸሎት መቅረብ አንችልም። (ያዕቆብ 1:5, 6) አምላክ እንዳለና እንደሚያስብልን እርግጠኞች መሆን ይኖርብናል። መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት እምነታችንን ማጠናከር እንችላለን፤ ምክንያቱም እውነተኛ እምነት በማስረጃና አምላክ በቃሉ ውስጥ ዋስትና በሰጠባቸው ተስፋዎች ላይ የተመሠረተ ነው።—ዕብራውያን 11:1, 6ን አንብብ።
የልባችንን አውጥተን በትሕትና መጸለይ ይኖርብናል። የአምላክ ልጅ ኢየሱስም እንኳ ይጸልይ የነበረው በትሕትና ነበር። (ሉቃስ 22:41, 42) በመሆኑም አምላክ ምን ማድረግ እንዳለበት እኛ ለእሱ ከመንገር ይልቅ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ መሥፈርቶቹን ለመረዳት መጣር ይኖርብናል። ከዚያም ከአምላክ ፈቃድ ጋር በሚስማማ መንገድ መጸለይ እንችላለን።—1 ዮሐንስ 5:14ን አንብብ።