በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥያቄዎችና መልሶቻቸው

አምላክ ሁሉንም ጸሎቶች ይሰማል?

አምላክ፣ ከየትኛውም ብሔር ቢሆኑ ሰዎች የሚያቀርቡትን ጸሎት ይሰማል። (መዝሙር 145:18, 19) ስለሚያሳስበን ማንኛውም ጉዳይ እንድንጸልይ ቃሉ መጽሐፍ ቅዱስ ያበረታታናል። (ፊልጵስዩስ 4:6, 7) ሆኖም አንዳንድ ጸሎቶች አምላክን አያስደስቱትም። ለምሳሌ ያህል፣ የተሸመደዱ ጸሎቶችን ደጋግሞ ማቅረብ አምላክን አያስደስተውም።—ማቴዎስ 6:7ን አንብብ።

በተጨማሪም ይሖዋ ሆን ብለው ሕጎቹን ችላ የሚሉ ሰዎች የሚያቀርቧቸውን ጸሎቶች ይጠላል። (ምሳሌ 28:9) ለምሳሌ ያህል፣ በጥንት ዘመን ነፍስ በማጥፋት ተጠያቂ የነበሩት እስራኤላውያን ያቀረቧቸውን ጸሎቶች ለመስማት ፈቃደኛ አልነበረም። ከዚህ በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው ጸሎታችን በአምላክ ዘንድ ተሰሚነት እንዲያገኝ ልናሟላቸው የሚገቡ የተወሰኑ መሥፈርቶች አሉ።—ኢሳይያስ 1:15ን አንብብ።

አምላክ ጸሎታችንን እንዲሰማ ምን ማድረግ ይኖርብናል?

ያለ እምነት ወደ አምላክ በጸሎት መቅረብ አንችልም። (ያዕቆብ 1:5, 6) አምላክ እንዳለና እንደሚያስብልን እርግጠኞች መሆን ይኖርብናል። መጽሐፍ ቅዱስን በማጥናት እምነታችንን ማጠናከር እንችላለን፤ ምክንያቱም እውነተኛ እምነት በማስረጃና አምላክ በቃሉ ውስጥ ዋስትና በሰጠባቸው ተስፋዎች ላይ የተመሠረተ ነው።—ዕብራውያን 11:1, 6ን አንብብ።

የልባችንን አውጥተን በትሕትና መጸለይ ይኖርብናል። የአምላክ ልጅ ኢየሱስም እንኳ ይጸልይ የነበረው በትሕትና ነበር። (ሉቃስ 22:41, 42) በመሆኑም አምላክ ምን ማድረግ እንዳለበት እኛ ለእሱ ከመንገር ይልቅ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ መሥፈርቶቹን ለመረዳት መጣር ይኖርብናል። ከዚያም ከአምላክ ፈቃድ ጋር በሚስማማ መንገድ መጸለይ እንችላለን።—1 ዮሐንስ 5:14ን አንብብ።