በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 23

ምሥራቹ ተሰራጨ

ምሥራቹ ተሰራጨ

ጳውሎስ በየብስና በባሕር ላይ እየተጓዘ ምሥራቹን ሰበከ

ጳውሎስ ወደ ክርስትና እምነት ከተቀየረ በኋላ ስለ አምላክ መንግሥት የሚገልጸውን ምሥራች በቅንዓት ማወጅ ጀመረ፤ በዚህም የተነሳ በአንድ ወቅት አሳዳጅ የነበረው ይህ ሰው ብዙውን ጊዜ ከባድ ስደት ይደርስበት ነበር። ደከመኝ ሰለቸኝ የማይለው ይህ ሐዋርያ፣ አምላክ ለሰው ዘር የነበረውን የመጀመሪያ ዓላማ ስለሚፈጽመው መንግሥት የሚገልጸውን ምሥራች ለማሰራጨት በተደጋጋሚ ጊዜያት ረጃጅም ጉዞዎች ያደርግ ነበር።

ጳውሎስ የመጀመሪያውን የስብከት ጉዞውን ባደረገበት ወቅት በልስጥራ የሚኖር ሲወለድ ጀምሮ ሽባ የሆነ አንድ ሰው ፈወሰ። በዚህ ጊዜ ሕዝቡ፣ ጳውሎስና የጉዞ ጓደኛው የሆነው በርናባስ አማልክት እንደሆኑ በመግለጽ መጮኽ ጀመረ። ጳውሎስና በርናባስ፣ የከተማው ሰው መሥዋዕት እንዳይሠዋላቸው ያስጣሉት በብዙ ችግር ነበር። ሆኖም የጳውሎስ ጠላቶች መጥተው ሲያግባቧቸው እነዚሁ ሰዎች ጳውሎስን በድንጋይ ወገሩት፤ ሕዝቡ የሞተ መስሏቸው ትተውት ቢሄዱም ሐዋርያው ከደረሰበት ጥቃት በሕይወት ተረፈ። ከጊዜ በኋላም ጳውሎስ ደቀ መዛሙርትን ለማበረታታት ወደዚያ ከተማ ተመለሰ።

ክርስትናን የተቀበሉ የተወሰኑ አይሁዳውያን፣ ከአሕዛብ ወገን የሆኑ አማኞች በሙሴ ሕግ ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ መመሪያዎችን መከተል እንዳለባቸው በመግለጻቸው ክርክር ተነሳ። ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም በመሄድ ይህንን ጉዳይ በዚያ ለሚገኙት ሐዋርያትና ሽማግሌዎች አቀረበላቸው። እነዚህ ወንድሞችም ቅዱሳን መጻሕፍትን በጥንቃቄ ከመረመሩና የአምላክን መንፈስ ቅዱስ አመራር ካገኙ በኋላ ጉባኤዎች ከጣዖት አምልኮና ከዝሙት እንዲርቁ እንዲሁም ደምም ሆነ ደሙ ያልፈሰሰ እንስሳ እንዳይበሉ የሚያሳስብ ደብዳቤ ጻፉ። እነዚህ መመሪያዎች “አስፈላጊ ነገሮች” ናቸው፤ እነዚህን መመሪያዎች ለመታዘዝ ግን የሙሴን ሕግ መጠበቅ አስፈላጊ አልነበረም።የሐዋርያት ሥራ 15:28, 29

ጳውሎስ ሁለተኛውን የስብከት ጉዞውን ሲያደርግ ወደ ቤርያ ሄደ፤ ቤርያ በአሁኑ ጊዜ የምትገኘው ግሪክ ውስጥ ነው። በዚያ ይኖሩ የነበሩት አይሁዶች ጳውሎስ ያስተማራቸው ነገር ትክክል መሆኑን ለማረጋገጥ በየዕለቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በመመርመር ቃሉን በታላቅ ጉጉት ተቀበሉ። በዚህች ከተማም ስደት በመነሳቱ ጳውሎስ ወደ አቴና ለመሄድ ተገደደ። ጳውሎስ በአቴና ለሚገኙ የተማሩ ሰዎች ያቀረበው ዘዴኛነትና ማስተዋል የተንጸባረቀበት አሳማኝ ንግግር በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው።

ጳውሎስ ሦስተኛውን የስብከት ጉዞ ካደረገ በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሰ። በዚያም ወደ ቤተ መቅደሱ በሄደ ጊዜ አንዳንድ አይሁዳውያን ሊገድሉት ስለፈለጉ ሁከት አስነሱ። የሮም ወታደሮች ጣልቃ በመግባት ጳውሎስን ከወሰዱት በኋላ መረመሩት። ጳውሎስ የሮም ዜግነት ያለው በመሆኑ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ በሮማዊው አገረ ገዥ በፊሊክስ ፊት ቀርቦ የመከላከያ መልስ ሰጠ። አይሁዳውያኑ በጳውሎስ ላይ ለሰነዘሩት ክስ ምንም ማስረጃ ሊያቀርቡ አልቻሉም። ጳውሎስ፣ ፊስጦስ በተባለው ሌላ ሮማዊ አገረ ገዥ ፊት ቀረበ፤ በዚህ ጊዜ ጳውሎስ፣ ፊስጦስ ለአይሁዳውያን አሳልፎ እንዳይሰጠው ለማድረግ ሲል “ወደ ቄሳር ይግባኝ ብያለሁ!” አለ። ፊስጦስም “ወደ ቄሳር ትሄዳለህ” ሲል መለሰለት።—የሐዋርያት ሥራ 25:11, 12

ከዚያም ጳውሎስ ችሎት ፊት ለመቅረብ በመርከብ ወደ ጣሊያን ተወሰደ። በጉዞው ወቅት መርከቧ ስለተሰበረች የክረምቱን ጊዜ በማልታ ደሴት ለማሳለፍ ተገደደ። በመጨረሻም ሮም ሲደርስ ለሁለት ዓመት ያህል በተከራየው ቤት ኖረ። ይህ ቀናተኛ ሐዋርያ በወታደር ይጠበቅ የነበረ ቢሆንም ወደ እሱ ለሚመጡት ሁሉ ስለ አምላክ መንግሥት መስበኩን አላቆመም።

በሐዋርያት ሥራ 11:22 እስከ 28:31 ላይ የተመሠረተ።