በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ክፍል 1

አምላክ ስለ እኛ ያስባል?

አምላክ ስለ እኛ ያስባል?

ዓለማችን በችግር የተሞላ ነው። ጦርነት፣ የተፈጥሮ አደጋ፣ በሽታ፣ ድህነት፣ ሙስናና ሌሎች ክፉ ነገሮች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ለሥቃይ ዳርገዋል። አንተም ብትሆን በየቀኑ የሚያስጨንቁ ነገሮች ያጋጥሙህ ይሆናል። ታዲያ ማን ሊረዳን ይችላል? ስለ እኛ የሚያስብ አካል ይኖር ይሆን?

አምላክ ለእኛ ያለው ፍቅር እናት ለልጇ ካላት ፍቅር ይበልጣል

አምላክ ከልብ እንደሚያስብልን እርግጠኞች መሆን እንችላለን። ምክንያቱም በቅዱስ ቃሉ ውስጥ እንዲህ ብሏል፦ “እናት የምታጠባውን ልጇን ልትረሳ ትችላለች? ከማህፀኗ ለወጣውስ ልጅ አትራራም? እነዚህ ሴቶች ቢረሱ እንኳ እኔ ፈጽሞ አልረሳሽም።” a

ይህን ማወቅ አያጽናናም? የሰው ልጆች ከሚያሳዩት እጅግ ጠንካራ እንደሆኑ ከሚታሰቡ ስሜቶች አንዱ እናት ለልጇ ያላት ፍቅር ነው፤ አምላክ ለእኛ ያለው ፍቅር ከዚህ ዓይነቱ ፍቅር እንኳ የላቀ ነው። አምላክ በፍጹም አይተወንም! እንዲያውም አምላክ አስደናቂ በሆነ መንገድ እየረዳን ነው። እንዴት? ደስታ ያለው ሕይወት ለመኖር ቁልፉ ምን እንደሆነ በመጠቆም ነው፤ ይህ ቁልፍ እውነተኛ እምነት ማዳበር ነው።

እውነተኛ እምነት ማዳበር ደስተኛ ያደርግሃል። እንዲህ ዓይነቱ እምነት ከብዙ ችግሮች የሚያድንህ ሲሆን ልታስወግዳቸው የማትችላቸውን ችግሮች ደግሞ መቋቋም እንድትችል ይረዳሃል። በተጨማሪም ከአምላክ ጋር እንድትቀራረብ ያስችልሃል፤ ይህም የአእምሮና የልብ ሰላም ይሰጥሃል። እንዲሁም ወደፊት በገነት ውስጥ ለዘላለም የመኖር አጋጣሚ ይከፍትልሃል!

ይሁን እንጂ እውነተኛ እምነት ሲባል ምን ማለት ነው? ልታዳብረው የምትችለውስ እንዴት ነው?

a ቅዱስ መጽሐፉን አውጥተህ ኢሳይያስ 49:​15ን ተመልከት። ቅዱስ መጽሐፉ በምዕራፎችና በቁጥሮች የተከፋፈለ ነው። ለምሳሌ ያህል፣ ኢሳይያስ 49:​15 ሲባል የኢሳይያስ መጽሐፍ 49ኛው ምዕራፍ፣ ቁጥር 15 ማለት ነው።